top of page

ኢንተርኔትን በመገደብ ኢትዮጵያ ከአፍሪካ 1ኛ ሆናለች

የኢንተርኔት አገልግሎት በመገደብ ኢትዮጵያ ከአለም 4ኛ፣ ከአፍሪካ 1ኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ ያስታወቀው ‹‹ፍሪደም ሃውስ››፤ በቴሌኮም መሰረተ ልማትም የሚፈለገውን ያህል ውጤት አላመጣችም ብሏል፡፡ መንግስት በበኩሉ፤ ሪፖርቱ የተዛቡ አሃዞችን የያዘና ርዕዮተ አለማዊ ትግል የሚታይበት ነው በማለት አጣጥሎታል፡፡ የሀገራትን የመረጃ ነፃነት በመገምገም አመታዊ ሪፖርት በማውጣት የሚታወቀው ተቋሙ፤ በ2016 ሪፖርቱ፡- ቻይና፣ ሶርያ፣ ኢራንና ኢትዮጵያ እንደየቅደም ተከተላቸው ኢንተርኔትን በመገደብ አለምን እየመሩ ነው ብሏል፡፡ ኢስቶኒያ፣ አይስላንድ፣ ካናዳና አሜሪካ ኢንተርኔትን ያለ ገደብ የሚጠቀሙ አገራት መሆናቸውን ሪፖርቱ ጠቁሟል፡፡ አፍሪካዊቷ ኡጋንዳ፣ ባንግላዲሽና ኮምቦዶያ ደግሞ በኢንተርኔት ላይ የሚያደርጉን ገደብ በመቀነስ ማሻሻል አሳይቷል ብሏል - ‹‹ፍሪደም ሃውስ››፡፡ የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ መሃመድ ሰኢድ፤ የተቋሙን ሪፖርት ተቀባይነት የሌለው ነው ብለዋል፡፡ ‹‹አሁን ኢትዮጵያ ውስጥ ኢንተርኔት ዝግ አይደለም” ያሉት ኃላፊው፤ ‹‹ሪፖርቱ በሀገሪቱ ያለውን ተጨባጭ እውነታ የማይገልፅና የሀገሪቱን የቴሌኮም እድገት የማንኳሰስ ርዕዮተ አለማዊ ትግል የሚታይበት ነው›› ሲሉ አብራርተዋል፡፡ “የቴሌኮም ዘርፉ በግል መያዝ አለበት ከሚል አቋም በመነሳት፣ የርዕዮተ አለምና የፖሊሲ ለውጥ ለማምጣት ነው የተፈለገው” ያሉት አቶ መሃመድ፤ የሀገሪቱ ቴሌኮም በመንግስት በመያዙ በዘርፉ ብዙ እድገት ተመዝግቧል ብለዋል፡፡ በ‹‹ፍሪደም ሃውስ›› ሪፖርት፤ የኢትዮጵያ የኢንተርኔት አገልግሎት 12 በመቶ ብቻ ነው ተብሎ የተጠቀሰው ሃሰተኛ ነው ያሉት ኃላፊው፤ እውነታው 16 በመቶ ነው ብለዋል። በተመሳሳይ የሞባይል አገልግሎት ሽፋን 43 በመቶ ተብሎ የተጠቀሰው የተዛባ መሆኑን ጠቁመው፤ አሁን 52 በመቶ መድረሱንና ይሄም ሀገሪቱን በዘርፉ ከአፍሪካ 2ኛ እንደሚያደርጋት ገልፀዋል፡፡ የሞባይል ዳታ ኢንተርኔት አገልግሎት መዘጋቱ ከኢንተርኔት አገልግሎት ጋር መገናኘት እንደሌለበት የገለፁት አቶ መሃመድ፤ ‹‹የሞባይል ዳታ አገልግሎት ተዘግቶ አይቀርም፤ ሁኔታዎች ታይተው በሚመለከተው አካል ውሳኔ ሲሰጥበት ይለቀቃል›› ብለዋል፡


Who's Behind The Blog
Recommanded Reading

Search By Tags

No tags yet.

Follow  ''ethiodailypost''

  • Facebook Social Icon
  • Twitter Social Icon
  • Google+ Social Icon
  • Instagram Social Icon
  • YouTube Social  Icon
  • RSS Social Icon
bottom of page